ዲላ ዩኒቨርሲቲ ከ "ኢንፎ ማይንድ ሶሉሽንስ" ጋር የስምምነት ሰነድ ተፈራረመ

ዲ.ዩ፦ ግንቦት 11/2015 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ ዲላ ዩኒቨርሲቲ "ኢንፎ ማይንድ ሶሉሽንስ" ከተባለ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ጋር በተመራቂ ተማሪዎች ዙሪያ አብሮ ለመስራት የሚያስችል የስምምነት ሰነድ መፈራረሙ ተገልጿል።
ማቴዎስ ሀብቴ (ዶ/ር )፣ በዲላ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ ጉዳዮች ም/ፕሬዝዳንት ተወካይ፤ የተጠቀሰው ድርጅት በተመራቂ ተማሪዎች ዙሪያ ከዲላ ዩኒቨርሲቲ ጋር በትብብር ለመስራት የውል ስምምነት ላይ መድረሱን ነው የገለፁት።
ድርጅቱ በተለይም ከ"ኢትዬ ጆብስ" (ከኢትዮጵያ ስራዎች) ማኅበር ጋር በመተባበር ለተመራቂ ተማሪዎች የተለያዩ ስልጠናዎችን እየሰጠ ከቀጣሪ ድርጅቶች ጋር በመስራት ለምሩቃን በስፋት እድሎችን እየፈጠረ እንደሚገኝ ተገልጿል።

የዲላ ዩኒቨርሲቲ መምህራንና ተመራማሪዎች በጣሊያን አገር ቱሪን ዩኒቨርሲቲ ጉብኝት አካሄዱ

ዲ.ዩ፦ ግንቦት 10/2015 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፥ በዲላ ዩኒቨርሲቲ እና በጣሊያን አገር የሚገኘው ቱሪን ዩኒቨርሲቲ የጋራ ትብብር ስምምነት አካል የሆነ የመምህራን ጉብኝት ተካሄደ። የዲላ ዩኒቨርሲቲ ሶስት መምህራንና ተመራማሪዎች ናቸው ከሚያዚያ 28 እስከ ግንቦት 11/2015 ዓ.ም የሚቆየውን ጉብኝት በቱሪን ዩኒቨርሲቲ እያካሄዱ ያሉት።
እንደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋም የዲላ ዩኒቨርሲቲ በተሰጡት ተልዕኮዎች ውጤታማ ለመሆን አገራዊና ዓለምአቀፋዊ ትብብሮችን ከተለያዩ ተቋማት ጋር እየተፈራረመ ይተገብራል። በጣሊያን አገር ቱሪን ዩኒቨርሲቲ እየተካሄደ ያለው የመምህራኑና ተመራማሪዎቹ ጉብኝትና ወይይትም የዚሁ አላማ አካል መሆኑ ነው የተገለፀው።

ለጌዴኦ ዞን ግብርና ባለሙያዎች በ"ጂ.አይ.ኤስ" የመረጃ አሰባሰብ ዙሪያ የክህሎት ማጎልበቻ ስልጠና ተሰጠ

ዲ.ዩ፦ ግንቦት 10/2015 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ የዲላ ዩኒቨርሲቲ ከጌዴኦ ዞን ጋር በመተባበር በ"ጂ.አይ.ኤስ" (GIS) አጠቃላይ ዲጂታል መረጃ አሰባሰብ ዙሪያ ለዲላ ዙርያ ወረዳ 17 የግብርና ባለሙያዎች የክህሎት ማጎልበቻ ስልጠና ተሰጥቷል።
በስልጠናው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት አለማየሁ አካሉ (ዶ/ር)፣ በዲላ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ም/ኘሬዝዳንት ጽ/ቤት ኃላፊ፤ ለምንሰራው ስራ በቂ ክህሎትና እውቀት መታጠቅ በእጅጉ አስፈላጊ በመሆኑ፤ ያለንን እና የጎደለንን ለመለየት ይህ ስልጠና ትልቅ አስተዋጾ አለው ብለዋል።
ዶ/ር አለማየሁ አክለው፣ ኘሮጀክቱ ጌዴኦ ዞን ምን ሀብት እንዳለው፣ ያለውን ሀብት እንዴት መጠቀም እንደሚችል፤ በለየ አኳኋን መረጃን በደንብ አደራጅቶና ሰንዶ ለመያዝ ጉልህ ሚና ይኖረዋልም ብለዋል።

በዲላ ዩኒቨርሲቲ የ2015 ዓ.ም ተመራቂ ተማሪዎች የሞዴል ፈተና መሰጠት ተጀመረ

ዲ.ዩ፦ ግንቦት 09/2015 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ ዲላ ዩኒቨርሲቲ ለ2015 ዓ.ም ተመራቂ ተማሪዎች ለመጀመሪያ ጊዜ በ"ኦንላይን" የታገዘና ለአገር አቀፍ የከፍተኛ ትምህርት መውጫ ፈተና የሚያዘጋጅ የሞዴል ፈተና መስጠት ጀምሯል።
ማቴዎስ ሀብቴ (ዶ/ር)፣ በዲላ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት ተወካይ፤ በመጪው ሐምሌ ወር በመንግስትና የግል የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በሀገር አቀፍ ደረጃ ይሰጣል ተብሎ እቅድ የተያዘለትን የከፍተኛ ትምህርት የመውጫ ፈተና በዩኒቨርሲቲው በብቃት ለመስጠት ሰፊ ዝግጅት ሲደርግ መቆየቱን ገልጸዋል።

የዲላ ዩኒቨርሲቲ ከፍተኛ አመራር ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶችን ተዘዋውሮ ተመልክቷል

ዲ.ዩ፦ ግንቦት 04/2015 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ በዲላ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ችሮታው አየለ (ዶ/ር) የተመራ ከፍተኛ የአመራር ቡድን በተቋሙ እየተከናወኑ ያሉ ልዩ ልዩ የመሠረተ ልማት ስራዎችን ጎብኝቷል።
በከፍተኛ አመራሩ ምልከታ መጀመሪያ በኦዳያአ ግቢ እየተሰራ ያለ የዩኒቨርሲቲውን አጠቃላይ ደህንነት፣ የተማሪዎች እና ሰራተኞች አገልግሎት አሰጣጥ የሚመለከቱ ዘርፎችን ደህንነትና መረጃ አያያዝ የሚያዘመንን የአይ.ሲቲ መሰረተ ልማት (Security Operation Center) ተጎብኝቷል።
በዘርፉ የግቢውን ድህንነት ለመጠበቅ፣ የተማሪዎች እና ሰራተኞችን መረጃ ለመቆጣጠርና እንደ ምግብ ቤት፣ ሬጂስትራር እና መሰል ከተማሪዎች አገልግሎት ጋር የተያያዙ ዘርፎችን የመረጃ ስርአት በተቀናጀ መልኩ ለማስተዳደር የሚረዱ የአይ.ሲቲ ልማቶች ያሉበት የአፈፃፀም ደረጃ ምልከታ ተደርጎባቸዋል።

በጌዴኦ ዞን ኮቾሬ ወረዳ ለሚገኙ አርሶ አደሮች በምርምር የለማ የቡና ችግኝ ተሰራጨ

ዲ.ዩ፦ ሚያዝያ 15/2015 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ በዲላ ዩኒቨርሲቲ የማሕበረሰብ አገልግሎትና አጋርነት ዳይሬክቶሬት በጌዴኦ ዞን ኮቾሬ ወረዳ ከ19 ቀበሌዎች ለተውጣጡ አርሶ አደሮች በምርምር የለሙ የቡና ችግኞችን አከፋፍሏል።
ደረጀ ክፍሌ (ዶ/ር) በዲላ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዝዳንት፤ ዩኒቨርሲቲው ከአስራ ሦሥት በላይ ለማህበረሰቡ ተደራሽ የሚሆኑ ፕሮጀክቶችን እየሰራ ለማህበረሰብ ግልጋሎት ተደራሽ እያደረገ መሆኑን ገልፀዋል።
ከእነዚህም መካከል በዘንድሮ ዓመት በኮቾሬ ወረዳ ሊሰራጭ ከታቀደው 80 ሺህ የቡና ችግኝ ውስጥ ለሚያዚያ ተከላ የደረሱ 63 ሺህ የቡና ችግኞች ለአርሶ አደሮች እንዲደርሱ መደረጋቸውን ዶ/ር ደረጄ ገልጸዋል።

በምዕራብ ጉጂ ዞን አባያ ወረዳ ለሚገኙ አርሶ አደሮች የቡና ችግኝ ተሰራጨ

ዲ.ዩ፦ ሚያዚያ 13/2015 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ በዲላ ዩኒቨርሲቲ የማህበረሰብ አገልግሎትና አጋርነት ዳይሬክቶሬት በምዕራብ ጉጂ ዞን አባያ ወረዳ አምስት ቀበሌዎች ለተውጣጡ አርሶ አደሮች በምርምር የለሙ የቡና ችግኞችን አሰራጭቷል።
ደረጀ ክፍሌ (ዶ/ር )፣ በዲላ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዝዳንት፤ ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር እና ከምርምር ስራዎች ባለፈ በርከት ያሉ የማህበረሰብ ተደራሽ ፕሮጀክቶችን ለአካባቢው ህብረተሰብ ተጠቃሚነት እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል።
ከእነዚህ መካከል በዘንድሮ አመት በአባያ ወረዳ ሊሰራጭ ከታቀደው 42 ሺህ የቡና ችግኞች ውስጥ ለሚያዚያ ተከላ የደረሱ 36 ሺህ የቡና ችግኞች በዛሬው ዕለት ለአርሶ አደሮች መሰራጨታቸውን ነው ዶ/ር ደረጄ የገለፁት።

ዲላ ዩኒቨርሲቲ የመውጫ ፈተናን ለመተግበር የሚያስችል የ"ኦንላይን" ፈተና አስተዳደር ስርአት አበለፀገ

ዲ.ዩ፦ ሚያዚያ 12/2015 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ ከያዝነው 2015 ዓ.ም ጀምሮ በአገር አቀፍ ደረጃ ይሰጣል ተብሎ እቅድ የተያዘለትን የከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎች የመውጫ ፈተናን ለመተግበር የሚያስችል የ"ኦንላይን" ፈተና አስተዳደር ስርአት ማበልፀጉን ዲላ ዩኒቨርሲቲ አስታወቀ።
የ"ኦንላይን" ፈተና አስተዳደር ስርአቱ (Online Examination Management System) በዲላ ዩኒቨርሲቲ የኮምፒውተር ሳይንስ መምህራን በልፅጎ የዩኒቨርሲቲው ማኔጀመንት አባላት በተገኙበት ይፋ ተደርጓል።
ችሮታው አየለ (ዶ/ር)፣ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት የከፍተኛ ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ተማሪዎች የመውጫ ፈተና እንዲወስዱ በተወሰነው መሰረት ፈተናው የተሳካ እንዲሆን ዲላ ዩኒቨርሲቲ ዘርፍ ብዙ ዝግጅት እያደረገ ነው ብለዋል።

በቡሌ ወረዳ ለሚገኙ አርሶአደሮች የቀርቀሃ ችግኝ ስርጭት ተካሄደ

ዲ.ዩ፦ ሚያዝያ 12/2015 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ በዲላ ዩኒቨርሲቲ የማህበረሰብ አገልግሎትና አጋርነት ዳይሬክቶሬት በጌዴኦ ዞን ቡሌ ወረዳ ለሚገኙ አርሶ አደሮች የቀረቀሃ ችግኝ ስርጭት አካሂዷል።
ደረጄ ክፍሌ (ዶ/ር) በዲላ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ኘሬዝዳንት፤ ከአምስት አመታት በፊት ጀጎ ላይ የነበረው የቀርቀሃ ደን የመጥፋት አደጋ አጋጥሞት እንደነበር አስታውሰው፤ ደኑን መልሶ ለማልማት የአምስት አመት ኘሮጀክት በመንደፍ ወደ ስራ በመገባቱን አሁን ላይ ወደ 4.5 ሄክታር የቀርከሃ ደን መልሶ ማልማት ተችሏል ብለዋል።

Pages