ዲ.ዩ፦ ሐምሌ 4/2015 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ በዲላ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዝዳንት ጽህፈት ቤትና የሀገረሰብ ጥናት ተቋም ከቱሪን ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር፤ በሁለቱ ዩኒቨርሲቲዎች ያለውን የትብብር ስራ አሁናዊ ሁኔታ የተመለከተ ውይይት ተካሂዷል። በውይይቱ ከሁለቱ ዩኒቨርሲቲዎች ትብብር የተገኙ ልምዶች ተዳስሰዋል። ዲላ ዩኒቨርሲቲ ከጣልያኑ ቱሪን ዩኒቨርሲቲ ጋር በምርምር፣ "ስታፍ-ተማሪ" ልውውጥና ሌሎች አካዳሚያዊ ጉዳዮች ዙሪያ የተለያዩ የትብብር ስራዎችን ሲሰራ ቆይቷል። ምስጋኑ ለገሰ (ዶ/ር)፣ በዲላ ዩኒቨርስቲ የምርምርና ስርፀት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ተወካይ፤ መድረኩን ከቱሪን ዩኒቨርሲቲ በአካል የተገኙትን ፕሮፌሰር ማውሮ ቶስኮን ጨምሮ በበይነ-መረብ ስብሰባውን ከጣሊያን በቀጥታ የታደሙ ባልደረቦቻቸው ብሎም የዲላ ዩኒቨርሲቲ የበላይ አመራሮችንና ተሳታፊ ተመራማሪዎችን እንኳን ደህና መጣችሁ በማለት መድረኩን ከፍተዋል። ዶ/ር ምስጋኑ በመክፈቻ ንግግራቸው፤ የትበብርና አጋርነትን አስፈላጊነት ገልጸው፤ በጥቂት የተጀመረው የዲላና ቱሪን ዩኒቨርስቲዎች ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ከፍ እያለ መምጣቱን፤ በማሳያነትም በሀገረሰብ ጥናት ተቋም በኩል እያደገ የመጣው ግንኙነትና አጋርነት በዩኒቨርሲቲ ደረጃ ከፍ ማለቱን አንስተዋል። አያይዘውም፤ የዲላ ዩኒቨርሲቲ የትኩረት አቅጣጫ በሆኑት እንደ ግብርና አይነት ዘርፎች ላይ አጋርነትን ይበልጥ ለማጠናከር ያለመ መድረክ መሆኑን አስገንዝበዋል። ችሮታው አየለ (ዶ/ር) የዲላ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት በበኩላቸው፤ መድረኩ ከጣሊያኑ ቱሪን ዩኒቨርሲቲ ጋር ቀደም ብለን የጀመርነውን ግንኙነት ለማጠናከር የሚጠቅም ነው ሲሉ ገልጸውታል። ዶ/ር ችሮታው በንግግራቸው፤ ዲላ ዩኒቨርሲቲ የሚገኝበት አካባቢ በቡና ምርት ከአገር አልፎ በዓለምአቀፍ ደረጃ የሚታወቀው የይርጋጨፌ ቡና መገኛ፤ የጌዴኦ ጥብቅ ደንን በ 'ዩኔስኮ' ለማስመዝገብ መልካም ሂደቶች እየተደረጉ ያለበት አካባቢ መሆኑን አንስተዋል። ይህ አካባቢያዊ ሥነ-ምህዳር የተለያዩ እፅዋቶችን ያቀፈ መሆኑ ለምርምር ምቹ ሁኔታን እንደሚፈጥርም ጭምር ፕሬዝዳንቱ አስረድተዋል። የዩኒቨርሲቲው የትኩረት አቅጣጫ በሆነው የግብርና ዘርፍ ጠንካራ የሆነ ግንኙነትና ትብብር ለመፍጠር እንደሚፈልጉ ገልፀዋል። ሀብታሙ ተመስገን (ዶ/ር)፦ በዲላ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዝዳንት በበኩላቸው፤ የዲላ ዩኒቨርሲቲ የእድገት ደረጃ ከመነሻው ጀምሮ ምን ይመስላል የሚለውን ግንዛቤ በሚያስጨብጥ መልኩ ገለጻ አድርገዋል። አያይዘውም በአሁናዊ የተቋሙ ሁኔታ በመማር ማስተማር፣ በምርምርና በማህበረሰብ አገልግሎትና አጋርነት ዙሪያ ያሉ አቅሞችን አስረድተዋል። የዩኒቨርሲቲው የትኩረት አቅጣጫዎች የሆኑትን፤ ግብርና፣ የተፈጥሮ ሐብት ጥበቃ፣ ጤና እና ትምህርትን ከግምት ውስጥ ባስገባ መልኩ የምርምር ስራዎችን ከፍ ወዳለ ደረጃ ማሻገር እንፈልጋለን ሲሉ ገልጸዋል። ከቱሪን ዩኒቨርሲቲ የሥነ-ሰብዕ ኮሌጅ የመጡት ፕሮፌሰር ማውሮ ቶስኮ፤ ዩኒቨርሲቲያቸው ከዲላ ዩኒቨርሲቲ ጋር ከአመታት በፊት አጋርነትን እንደጀመረ ገልጸው፤ በ"ተማሪ-ስታፍ" ልውውጥ (Student-Staff Exchange) ማዕቀፍ ስድስት የሦስተኛ ዲግሪ ተማሪዎች ትምህርታቸውን እየተከታተሉ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ፕሮፌሰሩ አክለውም ይህንን ግንኙነት በማጠናከር ከ"ተማሪ-ስታፍ" ልውውጥ ባሻገር በሌሎች ትልልቅ ፕሮጀክቶችና ምርምሮች፣ በተለያዩ የድህረ ምረቃ ትምህርት ቤቶች ማስፋት የሚቻልበትን ሂደት መፍጠር እንደሚያስፈልግ አንስተዋል። አቶ ተስፋፅዮን ጴጥሮስ፣ በዲላ ዩኒቨርሲቲ የሀገረሰብ ጥናት ተቋም ዳይሬክተር እና ተመራማሪ በበኩላቸው፤ በሁለቱ ዩኒቨርሲቲዎች መካከል ያለውን ግንኙነት በዩኒቨርሲቲ ደረጃ የማስፋት ትልቅ ዓላማ እንደነበረና፤ የተለያዩ ውይይቶች ከፕሬዝዳንቱና ሌሎች የሚመለከታቸው የበላይ አመራሮች ጋር ከተደረገ በኋላ ተቋማዊ የሆነ ግንኙነት እንዲፈጠር ታስቦ የተዘጋጀ መድረክ መሆኑን ገልጸውልናል። ይህን ግንኙነት ማስፋት እና ዲላ ዩኒቨርሲቲ ሰፊ የመስራት አቅም እንዳለው ማስተዋወቅ አብሮ ከመስራትም ባለፈ "ዩኒቨርሲቲያችንን አለማቀፋዊ የማድረግ ሂደትን የሚያግዝ" መሆኑንም አቶ ተስፋፅዬን አያይዘው ተናግረዋል። መድረኩን በበይነ-መረብ ከጣሊያን በቀጥታ የተሳተፉት ፕሮፌሰር አልፍሬዶ ፓውቺሎ ከቱሪን ዩኒቨርሲቲ ግብርና፣ ደንና ሥነ-ምግብ ሳይንስ ትምህርት ክፍልና የአጋርነት ኮሚቴ ፕሬዝዳንት፣ እንዲሁም ማኑኤላ ቺያሮቺ ከቱሪን ዩኒቨርሲቲ ዓለምአቀፍ ግንኙነት በበኩላቸው፤ ይህ ውይይት ከተለያዩ የትምህርት ክፍሎች ጋር የበለጠ ጠንካራ አጋርነት ለመመስረት የሚያስችል ነው ሲሉ ገልጸዋል። የተፈጠረውን አጋርነት በዲላ ዩኒቨርሲቲ በኩል በምን የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ አተኩሮ ቢሰራ አዋጭ ይሆናል የሚለውን ከተለያዩ የዩኒቨርሲቲው የትኩረት አቅጣጫ ከሆኑ የትምህርት ክፍሎች የመጡ ባለሙያዎችና ተመራማሪዎች አስተያየት ሰጥተዋል። ዲላ ዩኒቨርሲቲ የአረንጓዴው ምድር ዩኒቨርሲቲ